የአሜሪካ ቀዶ ሕክምና ባለሙያዎች በተሳካ ሁኔታ የአሳማ ኩላሊት ወደ ሰው ልጅ ማስተላለፍ ችለዋል። ንቅለ ተከላው በኩላሊት ሕክምና ዘርፍ ተስፋ ሰጪ ስኬት ተብሏል።
በመላው ዓለም ኩላሊት ለጋሽ ያጡ ወይም የኩላሊት ንቅለ ተከላ እስኪያገኙ ወረፋ የሚጠባበቁ በርካታ ናቸው። የአሜሪካ የሕክምና ባለሙያዎች የአሳማን ኩላሊት ወደ ሰው ልጅ ማሸጋገር መቻላቸው ለሕሙማን ተስፋ ነው።
የአሳማ ኩላሊት የተሰጠው ግለሰብ በሰው ሠራሽ ነፍስ ማቆያ መሣሪያ እየተደገፈ የነበረ አንጎሉ መሥራት ያቆመ (ብሬን-ዴድ) ነው።
ኩላሊቱ የተሰጠው ሰው ሕሊናውን ከመሳቱ በፊት የሰውነት ክፍሎቹን ለመለገስ ይፈልግ ነበር። ቀዶ ሕክምናው የተደረገውም በቤተሰቦቹ ፈቃድ ነው።
ኩላሊቱ የተወሰደው አሳማ ዘረ መል ላይ መሻሻል ስለተደረገበት ኩላሊቱ ወደ ግለሰቡ ሲተላለፍ ሰውነቱ እንዲቀበለው ማድረግ ተችሏል።
ይህ ንቅለ ተከላ ገና በሌሎች ባለሙያዎች አልተገመገመም። በሳይንስ መጽሔቶችም ገና አልታተመም። ባለሙያዎቹ ሥራቸውን ለግምገማ ያቀርባሉ ተብሎ ግን ይጠበቃል።
እስካሁን ድረስ እንደዚህ አይነት ሙከራዎች የተደረጉት በእንስሳት ላይ ነው። ይህ ሙከራ በሰው ልጅ ላይ ሲደረግ የመጀመሪያው ነው ማለት ነው።