በአሜሪካዋ ቴክሳስ ሂዩስተን ውስጥ በአንድ የሙዚቃ ፌስቲቫል መክፈቻ ላይ በታደሙ ሰዎች መካከል በተፈጠረ መጨናነቅና ግፊያ ቢያንስ የስምንት ሰዎች ህይወት በርካቶች ላይ ጉዳት መድረሱ ተነገረ።
የአደጋ ጊዜ ባለሥልጣናት እንደተናገሩት በፌስቲቫሉ ላይ በታደሙት በርካታ ሰዎች ወደ መድረኩ ለመቅረብ በተፈጠረ መገፋፋት መጨናነቅ ተፈጥሮ ነው አደጋው የደረሰው።
በዚህም ሳቢያ ስምንት ሰዎች ሲሞቱ አስራ አንድ ሰዎች ደግሞ የልብ ድካም ገጥሟቸው ወደ ሆስፒታሎች ተወስደዋል።
በዚህ 50 ሺህ ያህል ሰው በታደመበት ዝግጅት ላይ ከሞቱትና ከባድ ጉዳት ከደረሰባቸው ሰዎች በተጨማሪም 300 የሚሆኑ ሰዎች ቀላል የመቁሰልና የመላላጥ ጉዳት ደርሶባቸው ህክምና እንደተደረገላቸው ተነገሯል።
የሁዩስተን እሳት አደጋ መሥሪያ ቤት ኃላፊ የሆኑት ሳሙኤል ፔኛ እንደተናገሩት አደጋው ያጋጠመው አርብ ምሽት ከሦስት ሰዓት በኋላ ነበር።
“የተሰበሰበው ሕዝብ ወደ መድረኩ ለመጠጋት በሚገፋፋበት ጊዜ መጨናነቅና መደናገጥ ተፈጥሯል” ሲሉ ኃላፊው ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።
የተፈጠረው መጨናነቅና መረጋገጥ በሰዎች ላይ ጉዳት ሲያስከትል ከባድ መረበሽ ተፈጥሮ ጉዳት አስከትሏል ሲሉም ተናግረዋል ሳሙኤል ፔኛ።
የፌስቲቫሉ መስራች የሆነው ትራቪስ ስኮት ለአንድ ጋዜጣ እንደተናገረው ለ75 ደቂቃዎች መድረክ ላይ ሆኖ ሙዚቃውን ባቀረበበት ጊዜ ከተመልካቾች መካከል የስቃይ ድምጽ ይሰማ ስለነበረ በተደጋጋሚ ለማቋረጥ ተገዶ ነበር።