የጉግል አባት ድርጅት የሆነው አልፋቤት በማሳ ላይ በመሰማራት የእያንዳንዱን ተክል ሁኔታ መከታተል የሚችሉና የገበሬዎችን ሕይወት ማቅለል የሚችሉ ሮቦቶችን ለሙከራ ማቅረቡ ተሰምቷል። ሮቦቶቹ ከላይ ሆነው ተክሎቹን መከታተል የሚችሉ ሲሆኑ የተክሎቹን ተፈጥሮአዊ እድገትና ሁኔታ በማይነካ መልኩ ስራቸውን መስራት እንደሚችሉ ተገልጿል። ድርጅቱ እንዳስታወቀው ዋነኛው አላማቸው ተክሎችን በተመለከተ በቂና አስተማማኝ መረጃ መሰብሰብ ነው።
የፕሮጀክቱ መሪ የሆኑት ኤሊየት ግራንት ሲናገሩ ” እነዚህ ሮቦቶች የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ወደፊት የሚኖረንን የግብርናዘዴ ዘመናዊ እንደሚያደርገው እምነታችን ነው” ብለዋል። የምርምር ቡድኑ እንደገለጸው እነዚህን ሮቦቶች ወደ ሙከራ ማሰገባት ያስፈለገው በዓለም ላይ ያለውን የምግብ እጥረት ለመቅረፍና ዘላቂ በሆነ መልኩ የግብርና ውጤቶችን ለማዳረስ ነው። ነገር ግን አሁን ላይ ገበሬዎችና ትልልቅ የግብርና ድርጅቶች ያሏቸው መሳሪያዎች ይህንን ለማድረግ አላስቻሏቸውም።