የቴክኖሎጂ ፈጣሪው ኤለን መስክ በአጭር ጊዜ ውስጥ የዓለማችን 2ኛው ቢሊየነር ሆነ።መስክ የማይክሮሶፍቱን ቢል ጌትስን በልጦ ነው እዚህ ደረጃ ላይ የተቀመጠው።
የኤለን መስክ ሀብት በአጭር ጊዜ የተምዘገዘገው ቴስላ የተባለው የኤሌክትሪክ መኪና አምራች ኩባንያው በስቶክ ገበያ ከፍተኛ ጭማሪ ማሳየቱን ተከትሎ ነው።ይህ ድንገተኛ የሀብት ጭማሪ የኤለን መስክን የሀብት መጠን ከ7 ቢሊዮን ወደ 128 ቢሊዮን አድርሶታል።
የቢሊየነሮችን ዝርዝር የሚያስቀምጠው ብሉምበርግ እንደሚለው ከሆነ በዚህ ሰዓት ኤለን መስክን የሚበልጠው የዓለማችን ቁንጮ ሀብታም የአማዞኑ ጄፍ ቤዞስ ብቻ ነው።
ቴስላ የአሌክትሪክ አምራች በአሜሪካ የስቶክ ገበያ ትልልቆቹን 500 ኩባንያዎች ደረጃ በሚያስቀምጠው ኤስ ኤንድ ፒ (S&P 500) ዝርዝር እንደሚገባ ባስታወቀ በአጭር ጊዜ ውስጥ ነው የሀብት ግስጋሴው በአስደንጋጭ መልኩ ሽቅብ የወጣው።
የዚህን ዜና መውጣት ተከትሎ በርካታ ሰዎች የቴስላ መኪናን ድርሻ ለመግዛት ሽሚያ እንዲፈጠር አድርጓል። የቴስላ ኩባንያ ጠቅላላ ግምትም ግማሽ ትሪሊዮን ዶላር አድርሶታል። ይህን ተከትሎ ምንም እንኳ የኤለን መስክ ድርሻ በቴስላ ኩባንያ ውስጥ አነስተኛ ቢሆንም የሰውየው ሀብት ጣሪያ እንዲነካ ምክንያት ሆኗል።